FREEDOM 4 ALL ETHIOPIANS

FREEDOM,DEMOCRACY.JUSTICE.AND UNITY FOR ALL ETHIOPIANS …by DANIEL TESFAYE

ዘረኝነትን ሲያቆላምጧት “ብሔርተኝነት” አሏት

አንዳንድ ሰዎች በአክራሪ ብሔርተኝነትና በዘረኝነት መካከል፣ እንዲሁም በብሔር ልዩነት እና በዘር ልዩነት ላይ የተመሰረተ ፖለቲካዊ ስርዓት የተለያዩ ናቸው ሲሉ ይገርሙኛል። ነገር ግን፣ የብሔርተኝነትና ዘረኝነት ፅንሰ-ሃሳብ ፍፁም ተመሳሳይ ናቸው። የዓለም ታሪክን ስንመለከትም ብሔርተኝነትና ዘረኝነት በጭራሽ ተለያይተው አያውቁም። በዚህ ፅሁፍ የሁለቱን የብሔርተኝትና ዘርኝነት ፅንሰ-ሃሳብን ከታሪክ ጋር አቀናጅተን በዝርዝር እንመለከታለን።

በቅድሚያ “ዘረኛ” የሚለው ቃል “በዘር ምክንያት ለአንዱ የሚያደላ፣ ሌላውን የሚጎዳ፣ የዘረኝነት አስተሳሰብን፥ አመለካከትን የሚያራምድ” የሚል ፍቺ አለው። “ብሔርተኛ” ደግሞ “ለብሔሩ (ጎሳው) ብቻ የሚስብና የሚያደላ፣ በሌላ ላይ ጥላቻ የሚያሳይ” ማለት ነው። “ዘረኝነት” የዘረኛ አቋምን የያዘ አመለካከት ሲሆን፣ “ብሔርተኛ” ደግሞ የብሔርተኛ አቋምን የያዘ አመለካከት ነው። “ብሔር” የሚለው ቃል “አንድ ዓይነት ቋንቋ፣ ባህልና ስነልቦናዊ አመካከት ያለው፣ በታሪክ፣ በኢኮኖሚ፥…የተሳሰረና በተወሰነ ክልል ውስጥ የሚኖር ሕዝብ” የሚል ፍቺ አለው። “ብሔረሰብ” የሚለው ቃል ደግሞ “ከደም አንድነት ይልቅ በክልል፥ በቋንቋና በባህል አንድነት ላይ የተመሰረተ፣ የተለያዩ ነገዶች የተዋሃዱበት ማህብረሰብ” ማለት ነው።

በመሰረቱ፣ ዘረኝነት እና ብሔርተኝነት በአድልዎ ላይ የተመሰረቱ አመለካከቶች ናቸው። ሁለቱም ውስጥ ለራስ ዘር/ብሔር ማድላት፥ መደገፍና ክፍ ክፍ ማድረግ፣ የሌላን ዘር/ብሔር ደግሞ ማግለል፥ መለየትና መጥላት አለ። በዘረኝነትና ብሔርተኝነት ውስጥ ራስን መውደድ ብቻ ሳይሆን ሌሎችን መጥላት፣ ለራስ ማዳላትና መጥቀም ብቻ ሳይሆን ሌሎችን ማግለልና መጉዳት አለ። ስለዚህ ሁለቱም በተመሳሳይ የተሳሳተ አመለካከት ላይ የተመሰረቱ ናቸው።

ከዚህ በተጨማሪ፣ በዘረኝነት ላይ የተመሰረቱ ፖለቲካዊ ስርዓቶችን ታሪካዊ አመጣጥ ስንመለከት ደግሞ ዘረኝነትና ብሔርተኝነት የአንድ ሣንቲም ሁለት ገፅታዎች መሆናቸውን እንገነዘባለን። ምክንያቱም፣ በዘረኝነት ላይ የተመሰረቱ ፖለቲካዊ ስርዓቶች በሙሉ መነሻቸው አሳፋሪ ሽንፈት፣ አክራሪ ብሔርተኝነት እና የጎሳ ፖለቲካ ናቸው። “የጎሳ ፖለቲካ” ማለት ደግሞ “በዘር፥ በጎሳ፥ በብሔረሰብ ላይ የተመሰረተ ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ ነው።

በዘረኝነት ታሪካዊ አመጣጥ ዙሪያ ጥልቅ ትንታኔ በመስጠት የሚታወቀው “George M Fredrickson”፣ እስከ መካከለኛው ዘመን ድረስ በአውሮፓ “ዘረኝነት” (Racism) የሚባል ነገር ታይቶ እንደማይታወቅ ይገልፃል። እንደ እሱ አገላለፅ፣ የዘረኝነት ምልክት ለመጀመሪያ ግዜ የታየው በ13ኛውና 14ኛው ክ/ዘመን በስፔን ሲሆን እሱም አይሁዶችን ከሰይጣንና ባዕድ አምልኮ ጋር በማያያዝ ነበር የተከሰተው። ነገር ግን፣ በ16ኛው ክ/ዘመን የስፔን መንግስት ይህን የተሳሳተ አመለካከት በይፋ በማገዱ ተወግዷል። ከዚያ በኋላ፣ ዘረኝነት ማቆጥቆጥ የጀመረው በ17ኛው ክ/ዘመን ሁለተኛ አጋማሽ በአሜሪካ ነው። ለዚህ ደግሞ እ.አ.አ. በ1667 በደቡባዊ አሜሪካ ቨርጅኒያ ግዛት የጥቁር አሜሪካዊያንን ጉልበት ለመበዝበዝ የወጣው ሕግ ተጠቃሽ ነው። ይሁን እንጂ፣ ዘረኝነት ተንሰራፍቶ ከፍተኛ ደረጃ ላይ የደረሰው በ19ኛው ክ/ዘመን ማብቂያ ላይ ነው።

“George M Fredrickson” የ19ኛው ክ/ዘመን በአሜሪካና አውሮፓ የነፃ-መውጣት፣ የብሔርተኝነት እና የኢምፔሪያሊዝም (Emancipation, Nationalism and Imperialism) ዘመን እንደነበር ይገልፃል። በተለይ ከ1870 – 1880 ያሉት ዓመታት በምዕራብ አውሮፓ ሀገራት ለዘረኝነት መነሻ የሆነው የዘውግ ብሔርተኝነት (Ethnic Nationalism) በከፍተኛ ሁኔታ የተስፋፋበት ነበር። በዚህ ወቅት በጀርመን በርሊን የተፈረመው “The scramble of Africa” የተሰኘው አፍሪካን የመቀራመት ስምምነት የምዕራብ ሀገራት የአክራሪ ብሔርተኝነት ውድድርን አጥናክረው የቀጠሉበት እንደነበር፤ “…an assertion of the competitive ethnic nationalism that was existed among European nations” በማለት ግልፆታል።

በመጨረሻም፣ “Fredrickson” ዘረኝነት ጫፍ ደርሶ ጨቋኝ ፖለቲካዊ ስርዓት ለመሆን የበቃው በ20ኛው ክፍለ ዘመን እንደሆነ ይጠቅሳል። በዚህ ወቅት ከተፈጠሩት “በግልፅ ዘረኛ የሆኑ መንግስታት” (Overtly Racist Regimes) የሚባሉት በአሜሪካ፣ በጀርመንና በደቡብ አፍሪካ የነበሩት ናቸው። እነዚህ ዘረኛ መንግስታዊ ስርዓቶች በዘር ላይ የተመሰረቱ ጨቋኝ ሕጎችና መመሪያዎች ከማውጣታቸው በፊት በግልፅ ብሔርተኛ ቡድኖች ነበሩ፡፡ ይህን “Fredrickson” እንዲህ ሲል ገልፆታል፦

“racist principles were not fully codified into laws effectively enforced by the state or made a central concern of public policy until the emergence of what I will call ‘overtly racist regimes’ in the last century.”

ከላይ የተጠቀሱት በዘረኝነት የተመሰከረላቸው ፖለቲካዊ ስርዓቶች ፍጹም ተመሳሳይ የሆነ መሰረት አላቸው። እነሱም፣ አንደኛ፡- አሳፋሪ ሽንፈት (Humiliating defeat)፣ ለሽንፈቱ ሌሎች ብሔሮችን፥ ብሔረሰቦችን ተጠያቂ ማድረግ (Scapegoating) እና የአንድን ብሔር የበላይነትና ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሌሎችን ብሔሮች መብትና ነፃነት የሚገድቡ ሕጎችን ማውጣትና ተግባራዊ ያደረጉ ናቸው።

እንደ “Fredrickson” አገላለፅ፣ በአሜሪካ የዘረኝነት ስርዓት መዘርጋት የተጀመረው በደቡባዊ የአሜሪካ ግዛቶች ሲሆኑ ዋና መነሻ ምክንያቱ በበደቡባዊ አሜሪካ የሚገኙ ነጮች በአሜሪካ የእርስ-በእርስ ጦርነት ወቅት አሳፋሪ ሽንፈት ስለገጠማቸው እንደሆነ ይጠቅሳል። እነዚህ ነጭ አሜሪካዊያን በጦርነቱ ለደረሰባቸው አሳፋሪ ሽንፈት በጥቁሮች ላይ አሳብበዋል (Scapegoat)። በመጨረሻም፣ በ20ኛው ክ/ዘመን በአሜሪካ የከተሞች መስፋፋት በእርሻ ማሳዎች ላይ የሚውሉ ጥቁሮችን ለመቆጣጠር አመቺ ባለመሆኑና የጥቁሮችን ጉልበት ብዝበዛ ለማስቀጠል በዘረኝነት ላይ የተመሰረተ ሕግና ደንብ በማውጣት ተግባራዊ አደረጉ። በተመሳሳይ፣ ጀርመኖች በአንደኛው የዓለም ጦርነት ለጋጠማቸው አሳፋሪ ሽንፈት አይሁዳዊያንን ተጠያቂ አድርገዋል። ከዚያ በመቀጠል፣ አይሁዶችን በዘር በመለየትና በመነጠል የዘር ማጥፋት ጭፍጨፋ ፈፅመዋል። በመጨረሻም፣ የደቡብ አፍሪካ ነጭ ሰፋሪዎች በእንግሊዝ ጦር ለደረሰባቸው አሳፋሪ ሽንፈት ጥቁር ደቡብ አፍሪካዊያንን ተጠያቂ አድርገዋል። የእንግሊዝ ጦር ከደቡብ አፍሪካ ሲወጣ በዘረኝነት ላይ የተመሰረተ ፖለቲካዊ ስርዓት በመዘርጋት በጥቁሮች ላይ ግፍና በደል ፈፅመዋል።

በዘረኝነት ላይ የተመሰረተ ፖለቲካዊ ስርዓት የሚዘረጋው፣ አንድ ብሔር ወይም ሀገር በታሪክ ካጋጠመው አሳፋሪ ሽንፈትና ፀፀት ራሱን ለማውጣት ሲል በሚያራምደው የጎሳ ፖለቲካ ነው። በዚህ መሰረት፣ አንድ ብሔር፥ ሕዝብ ከዚህ ቀደም ካጋጠመው አሳፋሪ ሽንፈትና ቀውስ ራሱን ለማውጣትና በሌሎች ብሔሮች፥ ብሔረሰቦች ወይም ሕዝቦች ላይ የበላይነቱንና ተጠቃሚነቱን ለማረጋገጥ ጨቋኝ የሆነ ፖለቲካዊ ስርዓት ይዘረጋል። ዘረኝነት እንዲኖር የተለየ ቋንቋ፣ ባህልና ስነልቦናዊ አመካከት ያለው ማህብረሰብ መኖር አለበት።

ብሔርና ብሔርተኝነት በሌለበት ዘረኝነት ሊኖር አይችልም። የዘር ልዩነት ቢኖርም እንኳን በቋንቋ፣ ባህልና ስነልቦናዊ አመለካከት ተመሳሳይ በሆኑ ሕዝቦች መካከል ዘረኝነት ሊኖር አይችልም። ስለዚህ፣ ዘረኝነት እንዲኖር በቅድሚያ የቋንቋ፣ የባህልና የስነልቦናዊ አመለካከት ልዩነት መኖር አለበት። በመሆኑም፣ ዘረኝነት እንዲኖር በቅድሚያ ብሔርና አክራሪ ብሔርተኝነት መኖር አለበት። በዚህ መሰረት፣ ብሔርተኝነት እና ዘረኝነት የአንድ ሳንቲም ሁለት ገፅታዎች ናቸው።

በመጨረሻም፣ አሁን በሀገራችን የተዘረጋው በብሔር ላይ የተመሰረተ ፖለቲካ ስርዓት በዘረኝነት ላይ የተመሰረተ መሆኑንና አለመሆኑን ለማወቅ ከጥንት ጀምሮ በአማራና ትግራይ መካከል የነበረው የዘውግ በሔርተኝነት፣ የአፄ ሚኒሊክ ወደ ስልጣን መምጣት (የትግራይና ሸዋ ዘውዳዊ አገዛዝ)፣ እንዲሁም የሕውሃት የትግል ማኒፌስቶ እና ስለ አማራ ሕዝብ የነበረው አቋምና አመለካከትን በማየት በራሳችሁ መፍረድ ትችላላችሁ። ለዚህ ያግዛችሁ ዘንድ “Fredrickson” የዘረኛ ስርዓት ዋና መለያ ባህሪ ያለውን የመጀመሪያ መስፈርት በመጥቀስ ፅሁፌን እቋጫለሁ፡

ስዩም ተሾመ

ስዩም ተሾመ

Single Post Navigation

Leave a comment